Category Archives: ሀይማኖት

የዓለም ሃይማኖቶች እና ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት

አቤል ዋበላ

መግቢያ
አንቀጽ ፲፰
እያንዳንዱ ሰው የሐሳብ የህሊናና የሃይማኖት ነጻነት መብት አለው፤ ይህም መብት ሃይማኖቱን ወይም እምነቱን የመለወጥ ነጻነትንና ብቻውን ወይንም ከሌሎች ጋር በኀብረት በይፋ ወይም በግል ሁኖ ሃይማኖቱን ወይም እምነቱን የማስተማተር በተግባር የመግለጽ የማምለክና የማክበር ነጻነትን ይጨምራል፡፡
አንቀጽ ፲፱
እያንዳንዱ ሰው የሐሳብና ሐሳቡን የመግለጽ መብት አለው፤  ይህም መብት ያለጣልቃ ገብነት በሐሳብ የመጽናትንና ዜናን ወይም ሐሳቦችን ያላንዳች የድንበር ገደብ የማግኘትን፣ የመቀበልን ወይም የማካፈልን ነጻነትን ይጨምራል፡፡
እንዲህ ጎን ለጎን አጠጋግቶ ያሰፈራቸው ዓለም አቀፉ የሰብኣዊ መብቶች ድንጋጌ (UDHR) ነው፡፡ ይሁንና በድንጋጌው በቅደም ተከተል እንደመስፈራቸው ሲስማሙ አይሰተዋልም፡፡ በአንድ ያለማችን ክፍል ያለ የማመን መብቴ ተደፈረ የሚል ግለሰብም ሆነ ቡድን በሌላው የዓለማችን ክፍል የሚገኙ ሰዎችን የመናገር ነጻነት ሲደፈጥጥ ይሰተዋላል፡፡ ሌላው የመናገር መብቴ ገደብ የለውም የሚል ደግሞ የሌላውን ሰው የማመን መብት ሲጥስ እና በአማኒው እሴቶች ሲያፌዝ ተመልክተናል፡፡ ይህ እሰጥ አገባ በተለያዩ እምነቶች፣ በአማኞች እና እምነት የለሾች፣ ባስ ሲል ደግሞ አንድ እምነት አለን ብለው በሚናገሩ ቡድኖች መካከልም ይስተዋላል፡፡ በቅርቡ በሀገረ አሜሪካ በ‹ዩቲዩብ› የተለቀቀ አንድ ቪድዮን ተከትሎ በተነሳው ብጥብጥ ምክንያት ይህ ርዕሰ ጉዳይ  በዓለም ዙርያ መነጋገገሪያ ሆኗል፡፡ ዐሳብን በነጻነት መግለጽ እስከምን ድረስ ነው? እስከመቼ እምነቶች የነውጥ እና ሁከት መነሾ ምክንያት ሆነው ይቀጥላሉ? የሚሉ ጥያቄዎች በብዙዎች በሕሊናቸው እንዲያመላለሱ አድርጓል፡፡
በሀገራችን ዓለም አቀፉን ወጀብ የተከተለ ትርምስ ባይፈጠርም አንዳንድ ብልጭታዎች መታየታቸው አልቀረም፡፡ በተለይ ሁለቱ የየሀገራችን ሰፊ ተከታይ ያላቸው እምነቶች (እስልምናና ክርስትና) ‹‹ያለመሪ›› የሃይማኖት አባት በተቀመጡበት በዚህ ወቅት ጉዳዩ እጅግ አሳሳቢና የሰከነ ውይይትን የሚጠይቅ ነው፡፡ የኢሕአዴግ መንግስት በተለመደ ስልቱ እኔ ብቻ ላውራ ስለሚል ቄሱም ሼኩም የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ካህናት እንዲሆኑ ይፈለጋል፡፡በዚህም ምክንያት እንኳን በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ጉልህ ተጽዕኖ ያላቸው እምነቶች ይቅርና ሌላው ግለሰብም ይናገር፣ የተለየ አስተሳስብ ይኑረው፣ ያን ይገልጽ፣ ያንፀባርቅ ዘንድ አልተፈቀደለትም፡፡ ለዚህ ማሳያ እሩቅ ሳንሄድ ይህች ጦማር በኢትዮጵያ እንዳትነበብ የደረሰባት ተደጋጋሚ እገዳ ማሳያ ነው፡፡ ይህ ጽሑፍ ከሰው ልጅ መሠረታዊ እሱነቱ ጋር የተያያዙት እምነት እንዲሁም ዐሳብ መግለጽን እንዴት ማየት አለብን የሚለውን በመዳሰስ ለውይይት መነሻ የሚሆን ዐሳብን ለማቅረብ ይሞክራል፣ ለማብራራት የሚሞክረው ‘ይህ እምነት ልክ ነው፣ ያኛው ጸብ አጫሪ  ነው ወይም እምነቶች ሁሉ ልክ ናቸው የሚለውን ሳይሆን የተለያየ እምነቶች ያሉበት ሀገር (በተለይ ኢትዮጵያ) እንዴት ትኑር የሚለውን ይሆናል፡፡የውይይታችን ማጠንጠኛም ከዚህ ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር ተያያዥ በሆኑ ጉዳዮች ላይ እንደሚያተኩርም ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

መቻቻል እና የተዛባ ትርጉሙ
አብዮታዊ ዴሞክራሲ ካመጣብን ቃላትና የተዛቡ ዐሳቦች አንዱ  ‘መቻቻል’ ነው፡፡ ብዙ ጊዜ የእምነት ጉዳዮች ሲነሱ የመንግስት ሚዲያዎች ይህንን ቃል ደጋግመው በመጥራት ግጭቱን የሚያበርዱ ይመስላቸዋል፡፡ መቻቻል መቻቻል፣ መቻቻል፣. . . . ይህ ግን ከእምነቶቹ ዶግማ አንጻር ከተመለከትነው እጅጉን የተንሸዋረረ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በመሠረቱ ሁለት የተለያዩ የእምነት አስተምህሮዎች ሊቻቻሉ አይችሉም፤ ተቻቻሉ ከተባለም አንዱ አንዱን ካልጨቆነ በስተቀር ሌላ ሁለቱንም ያልሆነ ሦስተኛ አዲስ እምነት ነው የሚሆኑት፡፡ ይህ ለሌሎች ጉዳዮች ሊሠራ እንደሚችል የተለያዩ ንደፈ-ሐሳቦች ሰፊ ማብራሪያን ይሰጣሉ፡፡ ነገር ግን ብዙ አዝማናትን ለተሻገሩት በብዙ ክርክር ላለፉት እንደ ክርስትና እና እስልምና ካሉ እምነቶች ጋር ግን አይገጥምም፡፡ አንድ በሀልዎተ እግዚአብሔር በሚያምን እና ይህች ዓለም አስገኝ፣ ፈጣሪ የላትም ብሎ በሚያምን መካከል የተቀመጠ ዐሳብ ካለ ሌላ አዲስ አስተሳሰብ ነው፡፡ ለምሳሌ ፈጣሪ ሊኖርም ላይኖርም ይችላል ብሎ እንደ መጠርጠር ያለ፡፡ በክርስትና “እግዚአብሔር አንድ ልጁን ለሁሉ ቤዛ አድርጎ እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶታል” ሲል በእስልምና ደግሞ  በግልጥ “አላህ አይወልድም፣ አይወለድም” ይላል፡፡ ታዲያ የመንግስት ባለስልጣናት እንዴት ነው መውለድ እና አለመወለድን ለማቻቻል ጥረት የሚያደርጉት???
ይህንን እንደ ጥቁር ከሰልና እንደ ነጭ ወተት ያለ ልዩነት በማድበስበስ፣ ለእምነት ተቋማት ተቋማዊ ነጻነታቸውን በመስጠት በቡድን አሊያም በግል የፈለጉት እምነት እንዲከተሉ ከመፍቀድ ይልቅ የቄሳራዊ ጳጳስነት (Caesario papal) መንገድን መከተል ይዟል፡፡ ይህም እምነት ተቋማቱን በቀሚስ ለባሽ ካድሬዎች በእጅ አዙር ለመምራት የሚደረግ ጥረት ነው፡፡ በአደባባይ ለሚዲያ ቀለብ ይሆን ዘንድ የካህናትቱን መስቀል ሲሳለሙ እና በየመስኪዱ ሲሰግዱ በማሳየት እኛም በእምነት ጥላ ስር ነን (ምእመን ነን)  ለማለት ይሞከራል፡፡ ይህም በየእምነቱ፣ በአማንያን አለመመራት፣ ተቋማቱን በተገቢው መንገድ ለማስተዳደር ባለመቻላቸው  ምክንያት ብሶት፣ ቁጭትና ጥያቄዎች እንደፈጠሩ አድርጓል፡፡ ለዚህ እንደምሳሌ የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችን ጥያቄዎች ማንሳት ይቻላል፡፡
መንግስት አብዮታዊ ዴሞክራሲ ነው የምከተለው (አብዮታዊ ዴሞክራሲ በራሱ ከእምነቶች ጋር ብዙ የሚያላትም ገጾች ቢኖሩትም ዛሬ ከተነሳንበት ዐሳብ ጋር የሚሄደውን ብቻ ይዘን እንሄዳለን፡፡) ቢልም እምነቶችን በተመለከተ በሕገ መንግስቱ ላይ እንደሰፈረው “መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፤ ሃይማኖት በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም” ማለቱ በእምነቶች ላይ ያለው አመለካከት ኢ-ሃይማኖታዊ ሴኩላሪዝም (irreligion or secularism) መሆኑን በግልጽ ያሳያል፡፡ በዚህም ምክንያት ሃይማኖቶች ከብዙ መንግስታዊ አካላት (መንግስት ከሕዝብ ተነጥሎ እንደተለየ አካል ተቆጥሮ) ከአገልግሎት ሰጪ፣  ከትምህርት ተቋማት፣ ከመንግስት ሚዲያ ከመሳሰሉት. . .  ሲገለሉ በተግባር አይተናል፡፡ ብዙዎቻችንም የሁከት፣ የብጥብጥ ስጋት ስላለብን ጉዳዩን በዝምታ ይሁንታን አጎናጽፈነዋል፡፡ ይህም ለችግሮች መፍትሔ የመሆን አቅም ያላቸው የእምነት በጎ እሴቶች እንደአማራጭነት እንኳን እንዳይታዩ አስገድዷቸዋል፡፡
በመሠረቱ ሴኩላሪዝም እንደመድህን መቀበል ተገቢ አይደለም፡፡ በየትኛውም መስፈርት የኢ-ሃይማኖታዊነት (ሴኩላሪዝም) ሕይወት መርህ ሳይንሳዊ አይደለም፤ ሃይማኖታዊ የሕይወት ዘዬም እንዲሁ ሳይንሳዊ አይደለም፡፡ ሳይንስ;- ሴኩላሪዝም ከአማኒነት እንደሚሻል ማሳየት አይችልም ምክንያቱም ጉዳዩ ከሳይንስ በላይ (beyond science ) ነውና፡፡ የሃይማኖት ኀልዮት በአመክንዮ ጥያቄ ውስጥ ሊገባ እንደሚችል የታመነ ነው፡፡ ይህንንም ማድረግ፣ መጠየቅ የቅኖች መንገድ ነው፡፡   በሴኩላሪዝም እውነት እና በሃይማኖት እውነት መካከል ያለው ውዝግብ ግን በመደበኛ ሎጂክ ሊፈታ አይችልም፡፡ ይህ እውነታ በሁለት እምነቶች መካከልም ለሚካሄድ ክርክርም አይሰራም፡፡ የእስልምናን ስህተት ለማሳየት መጽሐፍ ቅዱስ (Christian scriptures) መጥቀስ እንደማለት ነው፡፡ለክርስቲያን መጽሐፍት ከቅዱስ ቁራን እና ሌሎች የበለጠ ስልጣን መስጠት ኢ-ምክንያታዊነት ነው፤ ከመጽሐፈ ሞርሞንም ቢሆንም የበለጠ የስልጣን የበላይነት የለውም፡፡
ይህ ሴኩላሪዝምን እንደገለልተኛ የማየት አካሄድ የተዛባ ነው፡፡ ምክንያም ሴኩላሪዝም ይህ ዓለም ከየት እንደመጣ እና ወዴት እንደሚሄድ የራሱ ትንታኔ አለው፡፡ ይህንን ካደረገ ከሌሎች ሃይማኖቶች ምን ለየው? ከጸበኞች መሀል አንዱን መርጦ ዳኛ አደርጎ መሾም ሲከፋ ደግሞ “እነዚህን አመጸኞች ግረፋቸው” ብሎ ልምጭ እንደመስጠት ያለ ነው፡፡ ሴኩላሪዝም የተውኔቱ አካል (entity) ነው እንጂ አዘጋጅ፣ አጋፋሪ ወይም ጸሐፌ ተውኔት ሊሆን አይገባውም፡፡ መንግስት ሴኩላሪዝምን እንደ ኀልዮት የማበረታታት መብት የለውም፤ በጉልበት ታንክ  ተደግፎ  ግን ተችሏል፡፡ ይህ ግን አላዋጣንም፡፡ ታሪካችንም ይህንን አያስተምረንም፡፡ ሀገሪቷ ጠንካራ ማኅበራዊ ጅማት ስላላት እንደሀገር መቀጠል ችላለች፤ ነገን ግን መተንበይ አንችልም፡፡
ከሴኩላሪዝም ባሻገር
ታዲያ ሴኩላሪዝም መፍትሔ ካልሆነ መፍትሔው ምንድን ነው የሚለውን ማጥናት ይገባል፡፡ በመሰረቱ ወደድንም ጠላንም አምልኮ ከሰው ልጅ ጋር የተሳሰረ፣ ከስሜት በላይ የሆነ አቅም ያለው ኃያል እንደሆነም ተረድተናል፡፡ብዙዎች ፍልስፍናን እና ሐሰሳን ለሕሊና ሰጥተው ለሃይማኖት ደግሞ ተረትን ይሰጣሉ፤ ከቀደሙት እጅግ የበዙት ደግሞ ሃይማኖት ፀረ-ሕሊና ወይም ህየንተ ሕሊና ሆኖ የሚቆም ነገር አይደለም፤ መልዕልተ ሕሊና ነው እንጂ ነው ይላሉ፡፡ ከሕሊና በላይ ነው እንደማለት፡፡ በዚህም ምክንያት ሃይማኖት እንደ ተበላ ዕቁብ የምንዘነጋው እንደ አረጀ አፈጀ ልማድ አሽቀንጥረን የምንጥለው ነገር አይደለም፡፡ ከዚህ ይልቅ የእምነትን መሠረታዊ ባሕርያት በማጥናት መፍትሔ መፈለግ ይበጃል፡፡
የትኛውም እምነት ሁለት መልኮች አሉት፤ የመጀመሪያው ይህች ዓለም ከየት እንደመጣች፣ ሰዎች በምድር ላይ እንዴት መኖር እንዳለባውቸውና ከሞት በኋላ ደግሞ ተስፋቸው ምን እንሆነ የሚያትት ነው፡፡ ይህም በየእምነቱ ሊቃውንት የሚተነተን ለተወሰኑ ሰዎች ብቻ የተለየ መብት (privilege) የሚሰጥ ሌሎችን የሚያገልል (exclusivist) የተንኳሽነት ባህርይ ያለው ነው፡፡ ይህም ሕዝብ  አሕዛብ፣ አማኒ ኢ-አማኒ፣ የተጠመቀ ያልተጠመቀ ብሎ የአዳምን ዘር የሚከፋፍል ነው፡፡ ይህ ልዩነት በመቀጠሉ በማኀበረሰቡ ውስጥ ከፍ ያለ ቦታ የሚያገኙ እና የገንዘብ ጥቅም የሚያገኙ የእንጀራ ገመዳቸው ከእነዚህ የእምነት ተቋማት ጋር የተሳሰረ ሰዎች ደግሞ ልዩነቱን የበለጠ እንዲሰፋ ተግተው ይሰራሉ፡፡እውቁ  ጸሐፊ ሰልማን ሩሽዲ  የቁጣ መፈልፈያ (outrage industry) የሚላቸው ዓይነት ነገር ናቸው፡፡ እነዚህ ኃይላት እምነትን የወግ አጥባቂዎች ማጎሪያ፣ የቁጡዎች መነሐሪያ፣  ኋላቀር፣  ማኅበረሰባዊነትን የሚንድ፣ ከሕሊና ውጪ ያለ (anti-rationale) ያደርጉታል፡፡
ሁለተኛው የእምነት ገጽ ደግሞ በተቃራኒው ሁሉን ሰብስቦ የሚያቅፍ፣ ስለሰብዓዊነት የሚሰብክ፣ የሰው ልጆችን የሚያስተሳስር ነው፡፡ ለበጎ ምግባር ሰውን የሚቆሰቁስ፣ ያጣው እንዲያገኝ፣ ያለው የበለጠ እንዲኖረው፣ የወደቀ እንዲነሳ፣ የታመመ እንዲድን፣ ለፍጹምነት ናፍቆት ያለው (nostalgic) ነው፡፡ በአጠቃላይ በነገረ መለኮት ዕውቀት ከመራቀቅ ይልቅ ስለፍቅር አብዝቶ የሚጨነቅ ነው፡፡  በእኛ ማኅበረሰብ ይህ መልክ የመጉላት አዝማማሚያ አለው፡፡ አቡነ ዘበሰማያት አንዴ መዝለቅ የማይችሉ ወይም “ያላህ ያረቢ አትበለን እምቢ” ብለው በእምነት ከማይመስላቸው ጋር ሳይቀር በፍቅር የሚኖሩ፤  ከአሕዛብ ጋር አትብላ! ከካፊር ጋር አትወዳጅ! የሚለውን ስብከት አልፈው (transcendence) ተካፍለው የሚበሉ ኢትዮጵያውያን ተቆጥረው አያልቁም፡፡ ሐዘኔታን የተላበሰ፣ ለድሆች የሚራራ፣ በደልን የሚጠየፍ ድሀ ሲበድል፣ ፍርድ ሲጓደል የሚቆጠቁጠው ነው፡፡ እንደማሕተመ ጋንዲ እና እማሆይ ትሬዛ ያሉ ታላላቆች ካልሆነ ብዙዎቹ የሃይማኖት መሪዎች ያልኖሩበት ነው፡፡
የእምነት ሰው ሁለቱንም መልኮቹን ይዞ የሚዞር ነው፡፡ አንደኛ ሲጎላ አንደኛው ደግሞ ሲደበዝዝ የሚኖር፡፡ በዚህም ምክንያት ዓለማችን ታንክና መድፍ በመስቀል የሚባርኩ ጳጳሳት፣ የጀሐድ ጦርነት የሚያውጁ ዑላማዎችን አስተናግዳለች፤ ብዙ ደም ፈሷል ብዙ ንብረትም ጠፍቷል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ሙሉ ሕይወታቸውን ለድሆች የሰጡ፣ ለፍትሕ እና ለእኩልነት የቆሙ፣ ድምፅ ለሌላቸው ምፃቸውን የሰጡ ደጋጎችንም አይተናል፡፡
ይህ መልክ እንዲለዋወጥ ምክንያት የሆኑ ብዙ የእምነቶቹ የውስጥ ጉዳዮችና ከሌላው ጋር (በሌላ የእምነት ጥላ ስር ካለው፣ ከኢ-አማኒው እንዲሁም ግራ ከገባው) የሚጋሯቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱና ዋነኛው ዐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ነው፡፡
ዐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ግንባር ቀደሙ እና የእምነቶቹን ሰላማዊነትን የሚቃኝ መልክ የሚያሲዝ ነው፡፡የመጀመሪያው እምነቶቹ በሕዝቡ ዘንድ በግልጽ እንዲነገሩ ዕድል ስለሚሰጥ የስማ በለው ደጋፊ አይኖራቸውም፡፡ሁሉም አውቆ እና ጠይቆ ስለሚረዳ እንደከብት የሚነዳውን ቁጥር ባያጠፋውም ይቀንሰዋል፡፡ ሁለተኛው ተገፋን እንዳናስተምር፣ እምነታችንን እንዳንመሰክር ተለከለን የሚል የእምነት ክፍል አይኖርም፡፡ ሐሳቡን በነጻነት የሚገልጽ እምነት፣ ነጻ የሆነ ህዝባዊ ምህዳሩን(public space) አቅሙ እንደፈቀደ ያለ አድሎ የሚጠቀም እምነት፣ ተቋማዊ ነጻነቱ የተጠበቀለት እምነት ለእኩይ ምግባራት ቦታ አይኖረውም፡፡ በዚህ ሂደት የእምነቶች መልካም ገጽ እያበበ ጸብ አጫሪነት እየከሰመ ይሄዳል፤ ፉክክር ካለም ለጽድቅ(ለእውነት) ይሆንና ማኀበረሰቡን የከበበው የቁስም ሆነ የመንፈስ  ድህነት ይወገዳል፡፡
ከሴኩላሪዝም ጋር ያለው ትልቁ ግጭት እዚህ ጋር ያለ ይመስለኛል፡፡ ሴኩላሪዝምን የአውሮጳ ስልጣኔ ምንጭ እምነትን ደግሞ የኋላቀርነት ምልክት የማደረግ አባዜ በመኖሩ ከላይ እንዳየነው ካለምንም ፍልስፍናዊ ዳራ (philosophical background) ሴኩላሪዝም ተቀባይነትን አግኝቷል፡፡ የአውሮጳ ስልጣኔ በመሠረቱ ከሴኩላሪዝም ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም፡፡ የአውሮጳ የስልጣኔ መንፈስ ምን እንደ ሆነ ለማሰረዳት ዶ/ር እጓለ ገብረዮሐንስ በፍልስፍና ካነሆለላቸው ሀይድልበርግ (Martin Heidegger) የኒቨርሲቲ እንደተመለሱ የጻፉትን መግለጹ ተገቢ ይመስለኛል፡፡
“በስነ ምግባር ረገድ የሰውን ጠባይና ችሎታ በመመርመር ከከፍተኛ የሞራል ሐሳብ ጽርየት ደርሰዋል፡፡ በማኀበራዊ ኑሮ ረገድ የእያንዳንዱ መብት እና ተግባር ተጠብቆ ሰው በንጹሕ ተምኔቱ መሠረት በሰላም ተደስቶ የሚኖርበትን የሕግ ውሳኔ አስገኝተዋል፡፡ በሀብት በንብረት በኩል ባነሰ ድካም ብዙ የሥራ ፍሬ በማስገኘታቸው ከራሳቸው አልፈው ለመላው ዓለም የሚተርፉ ሆነዋል፡፡ በሥነ ፍጥረት ዕውቀትና የእርሱ ዘርፍ በሆነው በቴክኖሎጂ ረገድ ከላይ እንደጠቀስነው የሰውን ሕሊና በጣም በማበልጸጋቸው ሰው ከሰውነት ድንበር ለማለፍ ምንም አልቀረው፡፡ በውበት ጥበባት ረገድ እነ ራፉኤልን ዳቢንቺን ሞዛርትን ቤቶሆቨንን ስመ ስማቸው ብቻ ብዙ ይናገራል፡፡ የአውሮጳ ስልጣኔ በአጭሩ ይሄ ነው፡፡ ባጭር ለመናገር ስንል ሳንበድለው አልቀረንም፡፡ ግን በሌላ ዕድል እንክሰዋለን፡፡
. . . .እሊህን የሕሊና ሕግጋት ወይም የስልጣኔ ፍሬዎች ያስገኙት አውሮጳውያን ናቸው፡፡ ግን እስያውያንም አፍሪካውያንም የራሳቸው ለማድረግ ይችላሉ፡፡ ዕውቀት ሲባል በጠቅላላ በማናቸውም ሰው ዘንድ በአምሳለ ዘርዕ ያለ ነገር ነው፡፡ ያንተም የኔም አይደለም፡፡ የሁላችንም ነው፡፡”
እውነታው ይሀ ሆኖ ሳለ የምዕራብ ክርስትና መምህራን ሴኩላሪዝም የእነርሱን ብዙ እሴቶች ገንዘብ በማድረጉ በቀጥታ እምነታችነን ተቀበል ከማለት ይልቅ ወደ ሴኩላሪዝም በማስጠጋት ቀስ በቀስ ወደራሳቸው የእምነት ጎራ ለማስገባት (በሰፈሩት ቁና መሰፈር አይቀርም እንዲሉ ወዳጅ ያደረጉት ሴኩላሪዝም እነርሱ ካበጁለት መስመር በማፈንገጥ ብዙ የምግባር እሴቶቻቸውን እንዲያጡ ሆኗል) ሙከራ ሲያደርጉ ተስተውሏል፡፡ይህም ሌሎች እምነቶች የከሸፈውን ሚሺነሪ በዘዴ ቀይረው መጡ እንዴ ብለው እንዲጠይቁም አስገድዷቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የመጠቃት ስሜት ሳለለ ከምዕራብ የመጣን ነገር ሁሉ እንደ ርኩስ የማየት ዘይቤ አለ፡፡ ይህ በልማት እና በዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ላይ አሻራው ጥሏል፡፡ ይህንን የመጠቃት ሰሜት በመላው ዓለም በሚገኙ ሙስሊሞች እና ምስራቃውያን ክርስቲያኖች (ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስያናትም ከዚህ ይመደባሉ) ይጋሩታል፡፡ ይህም እምነቶቹን ለመጠቀሚያነት ለሚያውሉ ሰዎች ምእመናንን ለእኩይ ዓላማ ለማሰለፍ እንዲችሉ ይረዳቸዋል፡፡ በመላው ዓለም የሚገኝ የትኛውም ሙስሊም አሜሪካ እና ምራባውያንን እንዲጠላ ተቀርጿል፡፡ ይህ አል ቃይዳን እና መሰል አሸባሪ (ይቅርታ አሸባሪ በኢትዮጵያ ሳይሆን በምዕራባውን ትርጉሙ ነው የተጠቀምኩበት) አባላትን ለም መሬት እንዲያገኝ ረድቶታል፡፡
የመላው ዓለምን ችግር የመፍታት አቅም ላይኖረን ይችላል፡፡ ሀገሪቱን ሴኩላር ማድረግ በእምነቶች መካከል ያለን ችግርንም ሆነ እምነቶች አመጡት የሚባለው ችግር ማስቀረት አይቻልም፡፡ ነገር ግን ሀገር በቀል የሆኑ መልካም እሴቶችን በመንከባከብ የብዙሐን ሀገር (pluralistic state) መገንባት እችላለን፡፡ በብዙሐን ሀገር የትኛውም እምነት ሆነ እምነት የለሽ በእኩል የሚታይበት ለጋራ እሴት ሰብኣዊነት በማስቀደም በኅብረት የሚሠራበት ነው፡፡ የተገፋ የእምነት ክፍል ስሌለ (ሁሉንም እምነት ከሚገፋው ሴኩላሪዝም በተቃርኖ) ለአክራሪነት ቦታ አይኖርም፡፡
የኢሕአዴግ መንግስት ግን በጀመረው የጥፋት ጎዳና መቀጠል  መምረጡን የምንረዳው እምነቶችን ከህዝባዊው ምህዳር ማግለሉ አንሶት ተቋማዊ ነጻነታቸውንም ለመስጠት ፍቃደኛ ባለመሆኑ ነው፡፡ Jo¨ rg Hausteina* and Terje Østebø  EPRDF’s revolutionary democracy and religious plurality: Islam and Christianity in post-Derg Ethiopia” የሚል ርዕስ በሰጡት ጥናታቸው ኢሕአዴግ በሃይማኖት ጉዳዮች ጣልቃ በመግባት ሕዝባዊውን ምሕዳር በማወኩ ምክንያት፣ በእምነቶች መካከል ሀገራዊ መግባባት በማራቁ ምክንያት እምነቶቹ የየራሳቸው የተለያየ የታሪክ ትርክት እንዲኖራቸው ማድረጉን ይገልጻሉ፡፡ ይህ ለሃይማኖት ጽንፈኝነት መምህራን ለመጽሐፋቸው ርዕስ ለሁከታው መቀስቀሻ እንደ የተቀበረ ድማሚት ያገለግላቸዋል፡፡  
ሌላው ሕሊችንን  ከፍ ከፍ ማድረግ የሚጠበቅብን ጉዳይ የእምነቶችን እሴቶች በተለመለከተ ነው፡፡ ሃይማኖቶች በጊዜ ሒደት ያበለጸጓቸው የራሳቸው እሴቶች አሏቸው፡፡ እነዚህ እሴቶች በዚያ በእነርሱ ወረዳ ለሌለ ሰው ትርጉም ባይሰጡም ለምእመናን ግን ትልቅ ዋጋ አላቸው፡፡ ብዙ ጊዜ ግን እምነትን የሚያሄሱ ሰዎች ይህንን ግምት ውስጥ አያስገቡም፡፡ ለሌሎች ተነጻጻሪ እሴቶች የሚያደርጉትን ጥንቃቄ ለእምነቶች እሴት ሲያደርጉ አይታይም፡፡ ለምሳሌ የአንድ ሕዝብ በዳሌ መጨፈር፣ ትከሻን ማውረግረግ፣ የአንዳንድ ድምጾች መደጋገም፣ ከትናጋ ጋር የሚጋጩ ድምጾች መብዛት የመሳሰሉ ነገሮች ያን ጎጥ ያስከፋሉ ተብሎ ስለሚታሰብ በእርሱ ላይ ላለመቀለድ ይሞከራል፡፡ ይህ ግን እምነቶች ላይ ሲደረግ አይስተዋልም፡፡ የሀገሪቱ መንግስትም ሴኩላር በመሆኑ ለእነዚህ የሰላም እሴቶች ድጋፍ እና ጥበቃን አያደርግም ይህም ለምንጓጓለት ሐሳብን በመግለጽ የሚያምንም ማኀበረሰብ ግንባታ እንቅፋት ሆኗል፡፡

ይህን ስናደርግ በእኔ እምነት “የክርስቲያን ደሴት” ወይም “ኢስላማዊት በሸሪአ የምትመራ ኢትየጵያን” ከመስበክ ይልቅ የጋራ ቅኝቶችን የሚደግፉና ለአዳዲስ አስተሳሰቦች በር የሚከፍቱ ቤተ እምነቶች ይኖሩናል፡፡ ነገር ግን እኛን የሚወክል ሀገራዊ ሁኔታዎችን ያገናዘበ ስርዓትን ተባብረን በሰላማዊ መንገድ ካልጠየቅን ምን አልባት በፈጣሪ ለማመን ፍቃድ መጠየቅ ሊኖርብንም ይችላል፡፡ በፈጣሪ መኖር አላምንም ብንል ደግሞ በፓርቲችን ማመን ግዴታህ ነው የሚባልበት ዘመን ሩቅ አይሆንም፡፡ጽሑፌን ሁሉን በሚያስማማው እና ‹‹በአንተ ላይ ሊደረግ የማትፈልገውን በሌላው አታደርግ›› በሚለው ድንቅ ዓረፍተ ነገር ስዘጋ ልቤን ደስ እያለው ነው፡፡

ሁለት ዓይን፣ ሁለት ዕይታ


ጊዜው ለውጡ ከተካሄደ አምስት ዓመት በኋላ ነበር፡፡ በወቅቱ የነበረው መንግስት ባጎናፀፈው የመወዳጀትና የመተባባር ባህል መሠረት ሃይማኖቶች ሕብረ ዝማሬ ያስተጋባሉ፡፡ የዱቤዎች ፈጣን ምቶችና የከበሮዎች ቀሰስተኛ ድለቃዎች ተደማምረው የራሳቸው የሆነ ሜሎዲ ፈጥረዋል፡፡ ዘማርያን በአንድ በኩል በሚያስረቀርቀው ድምፃቸው ዓለማቸውን ይቀጫሉ፡፡ መንዙማዎች በሌላ በኩል ያስተጋባሉ፡፡ ትላልቅ እንጨቶች የተጣለባቸው እሳቶች ይርመሰመሳሉ፡፡ ግቢው ጭስ በጭስ ሆኗል፡፡ ቄስና ሼህ አራጆች ሰንጋዎቻቸው ጥለው በትልቁ ጎራዴ ይበርካሉ፡፡ ደሞች በየአቅጣጫው ቦይ ፈጥረው ግቢውን ደም በደም አድርገውታል፡፡ የስጋ ዘለላዎች በተዘረጉት ቀጫጭን አጠናዎች ላይ ተዘርግተዋል፡፡ በሌላ አቅጣጫ ደግሞ የሀገሬውን የባህል ጭፈራና ዝማሬ በጋራ ሆነው ያቀልጡታል፡፡ ከግቢው ውጪ የፈረስ ውድድር እየተካሄደ ነው፡፡ ጎረምሶች የገና ዱላቸውን ይዘው የገና ኳሳን ይጠልዛሉ፡፡ ሰዎች በእያንዳንዱ ነገር የመሳተፍ ውዴታ ውስጥ ተጠምደዋል፡፡ ይህ ሁሉ ግርግር በአካባቢው ማኅበረሰብ ትብብር ተሰርቶ የተጠናቀቀው በደቡብ ሸዋ በሐይቆችና ቡታጀራ አውራጃ የሚገኘው መስጊድ ለማስመረቅ ነበር፡፡
አባቴ በዛን ወቅት በብሔራዊ ስሜት ነህሉሎ ነበር፡፡ ከፍተኛ የብሔራዊ ስሜት ጡዘት ውስጥ ገብቶ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ‹የአሞራ አገር ዋርካ፣ የእስላም አገር መካ› እንዳልተባለ አሁን ደግሞ ሙስሊሞች እንደክርስቲያን ወንድሞቻቸው እንደአንድ ዜጋ ተቆጥረዋል፡፡ እንደሌላው ጊዜ በተለየ ሁኔታ የመታየቱ፣ የማሽሟጠጡና በጎሪጥ የመመልከቱ ብሎም የመፀየፉ ስርዓት ካከተመ አምስት ዓመት ደፍኗል፡፡ አባቴ ለውጡ ባስከተለው የማኅበረሰብ ግንኙነት ምክንያት ተደስቶ ሴት ልጁን ‹ኢትዮጵያ› አላት፡፡ ባያውቀው ነው እንጂ ለልጁ ትልቅ የዕድሜ ልክ የቤት ሥራ ነበር የሰጣት – ነፍሱን ይማረውና፡፡ የሙስሊሞች እንደኢትዮጵያዊ በእኩል ዓይን የመታየት የቤት ሥራ፡፡ ይሄው የቤት ሥራው ሳይሠራ ፈተና ሆኖብን ምንም ለውጥ ሳይካሄድ እንዳለን አለን፡፡ በሁለት አቅጣጫ የተወጠረ ስስ ገመድ ይዘን አንዳች የአንዳችንን ከኢትዮጵያዊነት መዝገብ ለመፋቅ ጥረት አያደረግን፡፡ ይገርማል አባቴ በአፄዎቹ ጊዜ የነበረው ስርዓት ዳግመኛ ይከሰታል ብሎ ቢያምን ኖሮ ይህንን የዕድሜ ልክ የቤት ሥራ ከልጁ ዘንድ ባላስቀመጠ ነበር፡፡
ሙስሊሞች በኢትዮጵያውነታቸው ላይ የመለየት ሥራ የሚሰሩት መንግስታት ብቻ አይደሉም፡፡ የባለፉት መንግስታት ሰበካ ያጀሉ አንዳንድ የአፄው ዘመን አመለካከት ያላቸው በማኅበረሰቡ ውስጥ ተሰግስገው የጥላቻ አመለካከታቸውን በማኅበረሰቡ ላይ ያሰራጫሉ፡፡ እስቲ አንድ ታሪክ ላጫውታችሁ፡፡ ለታሪክ ሁሉ ነገር ታሪክ ነው፤ እዚህ አገር ከመወለዳችን በፊት ታሪክ፣ ከተወለድን በኋላ ታሪክ፣ አፈርም ስንለብስም ታሪክ፣ ሌላ የለንም ታሪክ፣ ታሪክ…፡፡ እዚህ ላይ ግን ኢትዮጵያ በድሮ ማንነቷ አንቱ ከሚባሉት ሀገራት ውስጥ አንዷ መሆኗን አልክድም ችግሩ ግን የድሮ ማንነት አሁን ባለንበት ሁኔታ ላይ ለመመንዘር ስንሞክር ነው፡፡

ወደ ታሪኬ ልግባ… በአንድ ወቅት እህቴ ‹ኢትዮጵያ› ትምህርቷን ለመማር አንድ ስሙን በማልጠቅሰው የትምህርት ተቋም ውስጥ የመመዝገብ ሂደት እያከናወነች ነበር፡፡ መዝጋቢው ዕድሜያቸው ጠና ያሉ ባጠቃላይ እምቢ አላረጅም ብለው እዛ ተቋም ውስጥ የቀሩ አዛውንት ናቸው፡፡ ለምዝገባ ስሟን ጠየቋት፡፡ መለሰችላቸው ‹‹ኢትዮጵያ አህመድ…›› ያደፈውን መነፅራቸውን ወደ ግንባራቸው ከፍ አድርገው የጥላቻ ንግግራቸውን አወረዱት ‹‹… ቆይ ቆይ አባትሽ ምን እየሰራ ነው?! ሁለት የማይቀላቀል ነገር ያቀላቅላሉ፡፡ ኢትዮጵያ ብሎ አሕመድ የማይሆን ነገር! ሰው እንዴት ዘይትና ውሃን ለማቀላቀል ይሞክራል?! ኤዲያ! ዛሬ ደግሞ ምንድነው የምታሰማኝ…›› ይህን ሁሉ ተብትበው ኢትዮጵያ ከአሕመድ ጋር ደብለው መመዝገቡን ግን አልተዉትም፡፡ ሥራቸው ነውና፡፡ ቆይ እስቲ ሰዎች ኢትዮጵያ ከአሕመድ ጋር ወዳጅነት መፍጠር አይችሉም እንዴ? መቼም ይህ ስያሜ የሚያስገርመው ክርስቲያኑን ብቻ አይደለም ሙስሊሙንም ጭምር እንጂ! አንዳንዱ አገሩን ከዚህ ውጪ አድርጎ የሚስል ‹‹ይቺ በምኗም ተምሳሌት የማትሆን አገር¡… እንዴት አባትሽ ይህንን ማንንም የማይወክል ገዳይ ስያሜ ያወጣልሻል?›› የሚለውን ጨረር ይለቃል፡፡ አንዳንዱ ደግሞ አፉን እያጣመመ ‹‹ተሃድሶ ተካሂዷል ማለት ነው!›› ይላል፡፡ አንድ ሰው ተወልዶ እትብቱ የተቀበረበት ያደገበትና ስንት ውጣ ወረድ ያሳለፈበት አካባቢ ብሎም አገር የመውደድ ተፈጥሮአዊ ግዴታ ያለበት ይመስለኛል፡፡ ሰው መቼም የተወለደበት አካባቢ ነውና የሚመስለው፡፡
የኢትዮጵያዊነት ስፌት
ሙስሊሞች በኢትዮጵያ ውስጥ በሌላ ዓይን መታየት ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡ በትንሹ አበበና አሕመድ ትምህርት ቤት ውስጥ ያላቸውን ቦታ ብንመለከት ለየቅል ነው፡፡ ያው አበበ በየመጽሐፍቱ ‹‹በሶ በላ!›› እንደተባለ ይዘከራል፡፡ አሕመድ ደግሞ በመማሪያ መጽሐፍት ውስጥ ምሳሌያዊ ቦታም የለውም፡፡ ስለዚህ አበበና አሕመድ ኢትዮጵያ ውስጥ ያላቸው እንድምታ የተለያየ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊና አረባዊ፡፡ በአንድ አገር ውስጥ ሁለት የተለያዩ ዜጎች አንዱ የእናት ልጅ ሌላው የእንጀራ እናት ልጅ ሆነው የሚታዩ መምሰል ከጀመሩ ቆይተዋል፡፡
በዚች እኛን ዜጎችዋን በምታስደምም አገር ሙስሊሞችን እንደመጤ የማየቱ እንድምታ ታውቆም ይሆን ሳይታወቅም በቀጥተኛ ወይም ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ ሲገለፅ ይስተዋላል፡፡ ቴዎድሮስ እንደአገር ገንቢ፣ አሕመድ ግራኝ እንደአገር አፍራሽ፡፡ ቴዎድሮስ ከቱባው የኢትዮጵያ አንድነት ጋር ሲገኛኝ በአንፃሩ ደግሞ አህመድ ግራኝ ወራሪና በታኝ የሚለውን የታሪክ ስያሜ ይለጠፍበታል፡፡ እነዚህንና የመሳሰሉትን እንድምታዎች ከቅርብ ክርስቲያን ዘመዶቻችን ሳይቀር ሲገለፅ ይታያል፡፡ እስቲ በአንድ ወቅት ከአንድ ወዳጄጋ ስለኢትዮጵያዊነት ስንጨዋወት የነገረኝን ላውሳላችሁ፡፡ በክርክራችን መሃል ወዳጄ ምርር ብሎ ማውራቱን ቀጠለ፡፡ ‹‹እኛ (ክርስቲያኖች) ከሳውዲ ስትሰደዱ ተቀብለን ስላስጠለልን ነው እንዲህ የምትሆኑት፤ የዛን ጊዜ በእንግድነት ባንቀበላችሁ እና ባናስተናግዳችሁ ኖሮ ኢትዮጵያዊ አትሆኑም ነበር›› አለኝ፤ በጣም ተናደድኩ ኢትዮጵያዊ ደም እያለኝ እንደ መጤ በመቁጠሬ በጣም ስሜታዊ ሆንኩ፡፡ ‹‹ቆይ ቆይ ወዳጄ! አንተ እያልከኝ ያለኸው መጤ ነህ ነው፡፡ በዛን ጊዜ ከአሁኗ ሳውዲ የመጡትን እንግዶች ተቀብለው በእንግድነት ያስተናገዱትኮ ያንተውም የእኔም አያቶች ነበሩ፡፡ ክርስትናም እስልምናም የመጡት ከውጭ ነው፤ ያንተም የእኔም አያቶች እዚህ ነው እትብታቸውን የቀበሩት! ማንም አረባዊ ማንም እስራኤላዊ አይደለም፡፡ እምነቱ ይለያይ እንጂ…›› አልኩት፡፡ ዕድሜ ለETV! በእኛ የኢድ በዓል እቺን የማትቀየር ኢትዮጵያዊና እስላማዊ ግኑኙነት ሁሌ እንደደሰኮረ ነው፡፡ ከዓመት ዓመት እንደዲሪቶ እየቀጣጠሉ አንዲት ሃባ የማይለወጥ የጃጀ ድስኮራ!! ይህ ድስኮራ በደንብ ስርዓት ባለው መልኩ በትክክለኛ መልዕክት ተላልፎ ሁሉንም ባኮራ ነበር፡፡ ነገር ግን የእያንዳንዱ ነገር ላይ ላዩ የሚያውቁት የETV ጋዜጠኞች በግልብ እያሉት እንደተለመደው ያልሆነ እንድምታ በማኅበረሰቡ ላይ ይፈጥራሉ፡፡
ኢትዮጵያዊነት በአፄዎቹ ጊዜ ሲሰፋ ሁሉን የኢትዮጵያ ቀለማት እንዳያካትት ተደርጎ ነው፡፡ ሕብረ-ቀለማዊነትን በማያስተናግድ በአንዲት ትንሽ ማንገቻ የታሰረ ትንሽዬ የሕፃን ቁምጣ፡፡ በአሁን ጊዜ ሁሉም ዜጎች እዛ ቁምጣ ውስጥ እራሳቸውን ሲከቱ ማንነታቸው በዜሮ የሚባዛበት የተንሸዋረረ ዜግነት ነበር፡፡ አንዳንዶቹ ይህን ትንሽዬ ኢትዮጵያዊነት እንደማያካትታቸው ሲያውቁ ሌላ ተቃራኒ ፅንፍ በመፍጠር ማንነታቸውን ያስከብራሉ፡፡ የተለያዩ የማንነት ፅንፎች መፈጠራቸው ለሀገሪቷ ዕድገት ማነቆ ነው የሚሆነው፡፡ “የተከበሩ ሟች  አባታችን” ‹‹የአክሱም ሃውልት ለወላይታ ምኑ ነው?!›› ነበር ያሉት፡፡ ይገርማል! ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከሰሜን እስከ ደቡብ ባለው የማንነት መገለጫ እንዲኮራ አባታዊ ምክር መስጠት ነበር ከመሪ የሚጠበቀው ፡፡ የአክሱም ሃውልት ለወላይታው የማንነት መገለጫ ካልሆነ፣ የላሊበላ አብያተ ክርስታኒያት ለሙስሊሞች እንደራስ ቅርስነት ካልታየ፣ የገዳ ስርዓት ለአማራው መኩሪያ ካልሆነ፣ የሐረር ግንቦችና  የነጃሺ መስጊዶች ለክርስቲያኑ እንደራሱ ቅርስ ካልተቆጠረ ኢትዮጵያ ምኗን አገር ሆነች፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያዊነት ሁሉኑም የሚያካትትና ኢትዮጵያውያን ደግሞ ሆደ ሰፊ ሊሆኑ ይገባል ባይ ነኝ፡፡
ወቅቱ በጃንሆይ ገዜ ነበር፡፡ ከጉራጌ ቀቤና የተገኙት የቃጥባሬ ሼህ ጥልቅ የሆነ ኢትዮጵያዊ ስሜት ነበራቸው፡፡ ይህንን ብሔራዊ ስሜት እምነቱ ውስጥ የተለያዩ እስላማዊ እንዲሁም ኢትዮጵያዊ የሆነ ማንነትና ባህል እንዲፈጥሩ አድርጓቸዋል፡፡ የቃጥባሬ ሼህ ኮፍያ ተመልክታችሁ ታውቃላችሁ? ኮፍያው ላይ ከሦስት የተለያዩ ቀለሞች ማለትም አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ የተዋቀሩ ሲሆን አምስት ክቦች ይታያሉ፡፡ አምስቱ ክቦች አምስቱን የእስምልና ማዕዘናት ሲያመለክቱ ሶስቱ ቀለማት ደግሞ ኢትዮጵያነት ያመለክታሉ፡፡ ይሄ ነው ኢትዮጵያዊነት በእምነት ውስጥ! ሁሉንም የሚያካትት! አሁንማ ሁሉም ጥግጥጉን ይዞ ሌላውን የማያካትትና ሌላውን ከአገራዊ አንድነት የሚፍቅ ተግባራት እያከናወነ በቃ የሚለው ጠፍቷል፡፡ አርቆ አሳቢ ድሮ ቀረ፡፡ ሁሉን ነገር ማጦዝ ነው በተንሸዋረረና ሁሉን በማያካትት እይታ….
ጊዜው ቴዎድሮስ ‹‹እምቢ ለአገሬ!›› ብሎ ራሱን የሰዋበትና አጤ ዮሐንስ በተገኘው አጋጣሚ ስልጣኑን ተረክቦ ሙስሊሞች ሃይማኖታቸውን በሀይል እንዲቀይሩ ከፍ ሲልም ያለ ርህራሄ የሚቀላበት ወቅት ነበር፡፡ በዛን ወቅት በጎጃም ሀገረ ገዢ የነበረው ይህንን አስገድዶ ክርስቲያን የማድረግ ዘመቻ በሚገርም ጥበብ ተወጣው፡፡ የሃይማኖት ቅየራው ሂደት የሚካሄደው በዋነኝነት ስጋ በማብላት ነበር፡፡ ሕዝበ ሙስሊም በተሰበሰበበት ቄሱ ከመጋረጃ ፊት ሼኩ ከመጋረጃ በስተኋላ ሆነው ሰንጋውን አጋደሙት፡፡ ከዛማ ከመጋረጃ በስተጀርባ የሚገኙት የሃይማኖት አባት በሬውን ሸልተው ከበጋረጃው ፊትለፊት ለሚገኙት የሃይማኖት አባት ማረጃውን አቀበሉት፡፡ ቄሱ ማረጃውን ወደ ላይ ከፍ አደርገውት ‹‹ይሄው በስመ አብ ብለን ባርከነዋል›› አሉ፡፡ ይህንን ሚስጥር የሚያውቁት ጥቂት የሃይማኖት አባቶችና ባለስለጣናት እንዲሁም የዛ አካባቢ የሙስሊም ማኅበረሰብ ነበር፡፡ ይሄ ነው ጥበብ፣ መተባበሩ በአካባቢው ማኅበረሰብ ለዘላለም ሲወሳ ይኖራል፡፡ ምንም አንኳን ከዛሬ 100 ዓመት በፊት ሙስሊሞችን ሃይማኖት የማስቀየር ስርዓት በቀጥተኛ መንገድ ቢገባደድም አሁንም ሙስሊሙን ሽባ የማድረግ፣ ሽባ አድርጎም ከሃይማኖቱም የማራቅ ሂደት እንደቀጠለ ነው፡፡ ቀጥሎ አንመልከተው፡-
ጭንቅላቱን በለው
እንደሚታወቀው እንደኢትዮጵያ ባሉ አገራት በአንድ ቤተሰብ ውስጥ አባት ያለው ሚና ከፍተኛ ነው፡፡ ለቤተሰቡ የመሪነት ሚና ይጫወታል፣ የገቢ ምንጭም ነው፣ ቤተሰቡን ከአደጋ ይከላከላል፣ ባጠቃላይ የቤተሰቡ ራስና ምሰሶ ነው ማለት ይቻላል፡፡ በአሁን ጊዜ በተለያዩ ምክንያቶች ሙስሊሙ የራሴ የሚለውን መሪ እንዳይኖረው ተደርጓል፡፡ መሪ ለመሆን ከፍ ከፍ የሚሉት ታዳጊ መሪዎች ጭንቅላቻቸው እየተመቱ ቤታቸው ይቀመጣሉ፡፡ ሌላው ደግሞ እንኳን አንድ ማኅበረሰብ ለመምራት ይቅርና አህያዎችን በሰልፍ መምራት የሚያቅተው ሰው የሸህና ሐጂ ካባ ይከናነብና የዚህ ከአፍሪካ በብዛቱ ሦስተኛ የሆነ ሕዝብ ባልፈለገው መልኩ ‹‹መሪ›› ተብሎ ይቀመጣል፡፡ በሌላ ወገን ከሃይማኖቱ አልፎ በሀገሪቱ ጉዳዮች ላይ የሁሉም አገር የሆነችን ኢትዮጵያ ወክሎ አገራዊ ሚና ይጫወታል፡፡ ይሄ ነው ሁለት የተለያየ ዕይታ… በሙስሊሞች በኩል የመሪነት ሚና እንዳይጫወቱ ተቋማቸው ሽባ ሆኗል፡፡ ይህ ተቋም ሕጋዊ ዕይታው ከአንድ ኩባንያ የማይተናነስ በየዓመቱ ፍቃዱን የሚያድስ ተቋም ነው፡፡ ከግዴታዎቹ ውስጥ በዋነኝነት በዓመት ሦስቴ ለበዓላት ራሱን ማሳየትና የማያውቁትን ፖለቲካ መዶስከር ነው፡፡ በሙስሊሞች ዘንድ አንድ ነገር ጠብ ማድረግ የተሳነው ተቋም፡፡ ከባለሙያዎች ይልቅ ባህላውያን የሚበዙበት ተቋም፡፡ ካለመሪ አንድን የአገሪቷ እኩሌታ የሚሆን ማኅበረሰብ ለመምራት ይቅርና አንድን ቤተሰብ መምራት አይቻልም፡፡ በአሁኑ ጊዜ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት ሙስሊሙ አውራው እንደተመታበት የንብ ቀፎ ተበታትኖ ይገኛል፡፡ ስለዚህ ሙስሊሞች ያለመሪ እንዳይቀሳቀሱ ተብትቦ የያዛቸው ገመድ ሊፈታ ይገባል፡፡
ወደ አንድ ጎን ያዘመሙ የሲቪል ሰርቪስ ተቋማት
እንደሚታወቀው አገራችን ኢትዮጵያ ሃይማኖትና መንግስትን መለያየት እንደመፍትሄ ተመለክታ ትግበራውን ከጀመረች እነሆ ግማሽ ምዕተ አመት ሊሞላን ጥቂት ነው የሚቀረን ቢሆንም በአሁኑ ሰዓት አንድ የመንግስት ተቋም ተሂዶ ስለአንድ ሃይማኖት የሚያመለክቱ ጥቅሶችንና ፎቶዎችን መመልከት የተለመደ ነው፡፡ አንዳንዴ የሰቀላ ፉክክር በግልፅ የሚካሄድ ከፍ ሲልም የሰቀሉት የሃይማኖት ጎራ ለማገልገል የተቆረጠ ነው የሚመስለው፡፡ አገሪቷ የምትመራው በዓለማዊ ሕግ ሆኖ ተቋማቱ ግን ሲወርድ ሲዋረግ የመጣውን ሃይማዎታዊ ማንነቱ እንደተጠበቀ ነው፡፡ ባጠቃላይ መለስተኛ የሃይማኖት ተወካዮች ይመስላሉ፡፡ ይህ ነው እንግዲ መገለጫው ወደ አንድ ጎን ያዘመሙ ነገር ግን ሁሉንም እናስተናግዳለን የሚሉ የመንግስት ዓለማዊ ተቋሞች፡፡ አንዳንዴ እንዲሁም የራሳቸውን የሚያቀነቅን ሲመጣ ነገሮች በሚያስገርም ፍጥነት ይጠናቀቃሉ፡፡ አመለካከታቸውን የማይደግፍ ሲመጣ ግን ጉዳዩን መጎተት፣ ማመናጨቅ ሲበዛም መሳደብ የራሳቸው ነው፡፡ ምንም እንኳን ባብዛኛው ኢትዮጵያዊ ፈሪሃ አምላክ መሆኑን ባልክድም አለማዊነት ሁላችንም የሚያግባባ መስሎ ይታየኛል፡፡
ተቋም የለሽ ማድረግ
ሙስሊሞች ተቋም የለሽ ማድረግ ከትልቁ መጅሊስ እስከ ትናንሽ መድረሳዎች ድረስ የዘለቀ ነው፡፡ እስላማዊ የሆኑ ተቋማት ሲቋቋሙ በጥርጣሬ ዓይን ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡ ለሙስሊሙ ስለየማይገሰሰው ሕገመንግስት ይሰበካል በሌላው ወገን ደግሞ የራሱን የሃይማኖት አጀንዳ እንዲያከናውን ባለሙሉ መብት ይሆናል፡፡ በቅርቡ በመቋቋም ሂደት ላይ እያለ ባልታወቀ ምክንያት የተቋረጠው የዘምዘም ባንክ በዐብይነት የሚጠቀስ ነው፡፡
መሠረተ ልማት ማሳጣት
ይህ ጉዳይ ለአንዳንዶቹ ላይዋጥ ይችላል ነገር ግን ሕዝበ ሙስሊሙን ከአፄዎቹ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ከመሠረተ ልማት ማራቅ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ ዓለም አቀፍ እስላማዊ ግብረሰናይ ድርጅቶች እንዳይገቡ በሩን መከርቸም የሌላው ዓለምአቀፍ የሚሽነሪዎች ተቋም እንዲገቡ የጥሪ ደውሉን በተደጋጋሚ መምታት የተለመደ ሆኗል፡፡ ባጠቃላይ ሙስሊሞች በመሠረተ ልማት አመካኝቶ የሚሽነሪዎች ሰለባ ማድረግ በግልፅ የሚታይ ጉዳይ ነው፡፡ ታዲያ ምን ይደረግ በንፁህ መጠጥ ውሃ እየተመጣ!
በሩን መከርቸም
እንደሚታወቀው እስልምና ዓለም አቀፋዊ ሃይማኖት ነው፡፡ በየትኛው የዓለም ቦታዎች እስልምና አይገኝም ማለት ይከብዳል፡፡ ሙስሊሞች ደግሞ የጋራ የሆነውን ችግሮቻቸውን በዓለም አቀፍ ስብሰባዎችና አጀንዳዎች ላይ ይፈታሉ፡፡ ይህ ዓለም አቀፋ እስላማዊ ግኑኙነት ከትንሽዋ ጅቡቲ እስከ ብዙ ሙስሊም ሕዝብ የሚገኝባት ኢንዶኔዥያ ያካትታል፡፡ ኢትዮጵያ ግን በብዛቱ ከአፍሪካ ሦስተኛ የሆነ የሙስሊም ሕዝብ እያላት በዓለም አቀፋዊ መገናኛ ብዙሐን ‹‹የክርስቲያን ደሴት ነኝ!›› ብላ በሩን ከዘጋች ሰነባብታለች፡፡ ሌላው ደግሞ ከግኑኙነቱ አልፎ የዓለም አቀፍ የግኑኙነቱ ኃላፊ ሲሆኑ ሙስሊሙ ግን ምንም ዓይነት ምልከታ እንዳያሳይ በማዕቀብ ታጭቋል፡፡ ማዕቀቡ መቼ ያበቃል? ዋናው ነገር ሠላም፣ ዋናው ነገር ጤና፣ ዕድሜ መስታወት ነው እናያለን ገና! ተብሎ የለ…
በመጨረሻም
እምነቶች ጌታቸውን የሚጠሩበት ስያሜ ወይም ቋንቋ ቢለያይም መሠረታቸው ግን አንድ ነው፤ እሱም በመልካም ፀባይ ያዛሉ፣ ከክፉ ምግባር ይከለክላሉ እንዲሁም ለራስህ የምትወደን ለወንድምህ እንድትወድ ያዛሉ፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ የሦስቱ አብርሃማዊ ሃይማኖች ቤት ናት ብዬ ብገልፀው ማጋነን አይሆንም፡፡ ሦስቱም በሰላማዊ መንገድ የራሳቸውን አሻራ የጣሉባት አገር ናት ኢትዮጵያ፡፡
የኢትዮጵያና የኢስላም ግንኙነት ከሌላው ሀገር በተለየ መልኩ የቆየ ነው፡፡ ኢስላም ለዓለም ከመሰበኩ በፊት ኢትዮጵያ ነው የከተመው፡፡ የሰላት ጥሪ አዛን ለመጀመሪያ ጊዜ ያስረቀረቀው የሐበሻ ልጅ የሆነው ቢላል ነው፡፡ እናትና አባታቸውን ያጡት ነቢዩ መሀመድ በኢትዮጵያዊው እናት እንደ እናት ክብካቤ ተደርጎላቸው አድገዋል፡፡ ነቢዩ መሐመድ መካና መዲና አልመች ሲላቸው ሙሉ እምነታቸው ኢትዮጵያ ላይ ጥለው ባልደረቦቻቸውንና ልጆቻቸውን ወደ ኢትዮጵያ ሰደዋል፡፡ እንግዳ ተቀባይ የሆነው የሀገራችን ሕዝብ ብቸኝነት እንዳይሰማቸው መልካም እንክብካቤና እምነታቸውን በነፃነት እንዲያከናውኑ ፈቅደዋል፡፡
እንደሚታወቀው ውጭ ያሉ አካላት የራሳቸውን ኢ-ኢትዮጵያዊ አመለካከት ለማስረፅ እስከ አሁን ያልተቀረፈው ድህነትና ድንቁርና መፍትሄ ዘየድን በማለት እየሰረጉ ይገኛሉ፡፡ ስለሆነም አንድነት ከሀይልም በላይ መሆኑንና ድህነትና ድንቁርናን ደግሞ በራሳችን ቀናኢ መፍትሄ አሻሽለን ልናሳያቸው ይገባል፡፡ ምክንያቱም ከውጭ የሚመጣ ‹‹መፍትሄ›› የራሱ የሆነ አሉታዊ ተፅዕኖ አለውና፡፡ በአንድነት ስንሠራ ነው ለውጥና ልማት የሚያመጣው ነገርግን ሁሉንም ያላማከለ ወደ አንድ ጎን የተንጋደደ ተግባር እንደ ግመሏ ጀርባ በአንድ ጎን ያበጠ ይሆናል፡፡ አንዱ አድጎ ሌላው ቢተኮስ ምንም ለውጥ ባያስከትልም እንኳን ያደገው ዕድገት ይገታል፡፡
በጽሑፌ ማገባደጃ ላይ በወሎ ክፍለ ጠቅላይ ግዛት ጎጃም በሚባለው አካባቢ በ1897 እ.ኤ.አ የተወለዱተ የታላቁን አሊም ሸህ ሰዒድ መሐመድ ሳዲቅ ድንቅ ንግግር ልጥቀስና ልሰናበት፡፡

‹‹ … እኛም የአንድ አገር ሕዝብ የሆነው ኢትዮጵያኖች፣ ያንድ ቤት ሰው ስለሆነ ደካሞች በኃይለኞች እንዳይደመሰሱ፡፡ ….የሰው ልጆች በአዕምሮ ተመስርተው እንዲኖሩ የተመሰረተውን ሀይማኖት ለመለያያ መሳሪያ ማድረጋችን ቀርቶ እንዲሁ እንደተጀመረው መተሳሰራችን እየበረታ እንዲሄድና ለራስህ የምትወደውን ለወንድምህ አድርግ በተባለው መሠረት እርስ በርሳችን ተፋቅረን ያለው ለሌለው አካፍሎ… ያልተማረው ተምሮ ሕግን አክባሪ እንድንሆን እንመኛለን…›› ~ (ደሴ ከኢድ አልፈጥር ሰላት በኋላ በ3/6/1954)
—–
ጸሐፊውን ለማግኘት የኢሜይል አድራሻቸው የሆነውን ezunaa@facebook.com ይጠቀሙ::