ነፃነት እና ዳቦ

በሚሰሩበት ቦታ፣ በሚኖሩበት ሰፈር ወይም አንድ ካፌ ውስጥ ቁጭ ብለው አጠገብዎ የተቀመጡ ወጣቶች ስለ እንድ ፖለቲካ ነክ ጉዳይ አንስተው ሲወያዩ ይሰማሉ እንበል፡፡ የሚወያዩበት ጉዳይ አሁን በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት የሚያስከፋ እንደሚሆን ከገመቱ፤ ወጣቶቹን ‹የቀበጡ ለት› በሚል ዕይታ ገርመም ያደርጓቸዋል ወይም እራስዎትን ከቦታው ‹አልሰማሁም› በሚል እንድምታ ያሸሻሉ አልያም የሚራራ ልብ ካልዎት ለልጆቹ ይፈሩላቸዋል – እርስዎ እንደሰሟቸው የመንግስት ሰው (‹‹ጆሮ ጠቢ››) ቢሰማቸው ሊደርስባቸው የሚችለውን እያሰቡ፡፡ ፖለቲካ ነክ አይነት ውይይቶች ላይ የሚሳተፍ የቅርብ የሆነ ሰው ካልዎት ይመክራሉ፣ ይገስፃሉ፡፡ ምክርዎትን ለማጠናከር ምሳሌ አያጡም፡፡ በሀገሪቱ ጉዳይ ያገባናል ብለው የመንግስትን ውሳኔ ተቃውመው፣ የልዩነት ሃሳባቸውን በማሰማታቸው ብቻ ለእንግልት፣ ከኢኮኖሚ ዕድሎች የመገለል እና ግፋም ሲል ለእስራት የተዳረጉ ዜጎች ብዙ ናቸው፡፡ ‹ምን አጥተሽ ነው?› ሲሉ ይጠይቋታል በሀገሪቱ ፖለቲካ ንቁ ተሳታፊ (informed active participant) የሆነች ወዳጅዎትን፡፡ ‹ስራ አለሽ፤ በልተሽ ካደርሽ እና ከእኛ ጋር ማሕበራዊ ግንኙነት እንዳታደርጊ ማንም ካልከለከለሽ፤ ምን ይሁን ብለሽ ነው ከማትችይው ጋር የምትጋፊው? ደሞ ብቻሽን ለውጥ ላታመጪ! ለኛ ጭንቀት ነው ትርፉ› በማለት አርፋ ብትቀመጥ የተሻለ መሆኑን ይነግሯታል፡፡

በነፃነት ሃሳብን የመግለፅ (ወይም የሌላ አይነት ነፃነት) እጦት እራሱን ከሚያሳይባቸው መንገዶች አንዱና ዋነኛው ዜጎች በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ንቁ ተሳታፊ መሆን የሚያስከፍላቸው ዋጋ ከፍተኛ እንደሆነ ተገንዝበው፥ ግላዊ የሆነ ጭቆና እስካላጋጠማቸው ድረስ የተፈቀደላቸውን ብቻ እየተናገሩ/እየፃፉ/እያደረጉ ተቆጥበው መኖርን መምረጣቸው ነው፡፡

አከራካሪውን የቅደም ተከተል ጉዳይ ወደ ጎን ትተን ነፃነትንና ብልፅግና ሁለቱም እንደሚያስፈልጉን ግልፅ ነው፡፡ የነፃነት ጫፍ የተረጋገጥባት ነገር ግን ሰዎች ከዕለት ጉርሻ እጦት በየዕለቱ የሚረግፉባት ሀገር እንዲኖረን የማንመኘውን ያክል ዜጎች ችጋር የሚባል ነገር ሲነገር ብቻ የሚሰሙባት ነገር ግን መንግስት የሚናገሩትን፣ መስራት የሚችሉትን ወይንም ለአጠቃላይ እንቅስቃሴያቸው ልኬት አበጅቶ ጥሩ ከሚቀለብ የቤት እንስሳ የማይለዩበት ሀገር እንዲኖረን ፈዕሞ አንፈልግም፡፡

መጀመሪያ ራሴን ልቻል ወይስ መጀመሪያ ራሴን ልሁን?

ከነፃነት ይልቅ ቁሳዊ ብልፅግናን የሚያስቀድሙ ሰዎች በመከራከሪያቸው የሰው ልጆች ነፃነትን ማክበር የሚቻልበት ደረጃ ላይ ለመድረስና ዘላቂነቱንም ለማረጋገጥ ከድህነት ለመውጣት ቁልፍ የሆነውን ኢኮኖሚያዊ እድገትን ማረጋገጥ እንደ ቅድመ ሁኔታ ያስቀምጣሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ፍፁም አምባ ገነናዊ ወይም ለዘብተኛ አገዛዞች (Authoritorian regimes) ዲሞክሪያሲያዊ ከሆኑና መሰረታዊ ነፃነቶችን ከሚያከብሩ ስርአቶች ይልቅ የኢኮኖሚ እድገትን ለማረጋገጥ የተሻለ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥሩ ለማሳመን ይሞክራሉ፡፡ ስለዚህም የኢኮኖሚ እድገት እስኪመጣ ድረስ የሚታጣው በሀገሪቷ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ የመሳተፍ ነፃነት፣ የመደራጀት ነፃነት፣ የነፃና ፍትሃዊ ምርጫዎች አለመካሄድ፣ ወዘተ… ለብልፅግና የሚከፈል መስዕዋትነት ተደርጎ እንዲቆጠር ይፈልጋሉ፡፡

አምባ ገነናዊ ስርአት ኢኮኖሚያዊ ብልፅግናን ለማምጣት የተሻለ ምቹ ሁኔታ እንዴት ይፈጥራል?

የዚህ መከራከሪያ ፅንሰ ሐሳብ የሰው ልጆችን  የሚስለው በተፈጥሮ ሰነፍ እነደሆኑ አድርጎ ነው፡፡ ሰዎች የተሻለ ውጤት ያለው ስራ የሚሰሩት በጠንካራ ቁጥጥር ስር ሆነው ሲሰሩ ብቻ ስለሆነ ይህንን ከግንዛቤ በመክተት መንግስት በዜጎቹ ላይ ከብረት የጠነከረ የስራ ሥነ-ምግባርን ለማስረፅ መስራት አለበት፡፡ የዜጎችን ነፃነት ማክበር/ማስከበር ለእድገት ‹አስፈላጊ› የሆነውን የስራ ሥነ-ምግባር ለማስረፅ መንግስት ለሚወስዳቸው እርምጃዎች እንቅፋቶች ይሆናሉ፡፡ ስለዚህም መንግስት አስፈላጊ ብሎ ባመነበት ወቅት ሁሉ ከኪሱ እያወጣ የሚጠቀምበት ልክ የለሽ ሀይል ያስፈልገዋል፡፡

ዲሞክራሲያዊ የሆኑ ስርአቶች በአንፃሩ ልፍስፍሶች ናቸው፤ እንደብልፅግናን የሚያስቀድሙ ሰዎች መከራከሪያ ከሆነ፡፡ በዲሞክራሲያዊ ስርአት ውስጥ ስልጣንን ለመቆጣጠር የብዙሃኑን ድምፅ ማግኘት ግድ ስለሚል ስልጣን ላይ መውጣት/መቆየት የሚፈልግ ሃይል የብዙሃኑን ድጋፍ ለማግኘት ሲል ተወዳጅ (popular) የሆኑ ፖሊሲዎችን ይመርጣል፡፡ ለአጭር ጊዜ ህዝቡን ማስደሰት የሚችሉት እነዚህ ፖሊሲዎች የረጅም ጊዜ ውጤት ግን እድገትን የሚያበረታታ አይደለም፡፡ ለምሳሌ አብዛኞቹ ተወዳጅ የሚባሉት ፖሊሲዎች ለዕድገት አስፈላጊ የሆነውን ሃብትን ከማከማቸት ይልቅ ፍጆታን የሚያበረታቱ ናቸው፡፡

‹‹ነፃ አስተሳሰብ ለተሻለ ሕይወት!›› (ሬዲዮ ፋና)

በሌላ በኩል ነፃነት አስቀድሞ ያስፈልገናል የሚለው መከራከሪያ ማዕከል የሚያደርገው  የሰው ልጆች የበለጠ ውጤታማ ስራ መስራት የሚችሉት በነፃነት ማሰብ እና መስራት ሲችሉ መሆኑን ነው፡፡ የሰው ልጆች የህልውናቸው መገለጫ የሆነውን ነፃነታቸውን ተገፍፈው ውጤታማ የሆነ ስራ ሊሰሩ አይችሉም፤ ነፃነት ከሌላቸው የተሻለ የፈጠራ ስራ ሰርተው የተሻለ ነገን ለመኖር ማበረታቺያ አይኖራቸውም፡፡ ያላቸውንም ሃብትንም በአጭር ጊዜ ጥቅም በሚያስገኝላቸው ትርፋማ ስራ ላይ ብቻ ያውሉታል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን በሚያስተዳድራቸው መንግስት ላይ አመኔታን ያጣሉ፡፡ የተሻለ ምርታማ እና የአዳዲስ ግኝቶች ፈጣሪ የሆኑ የኢኮኖሚው እድገት አቀላጣፊ ዜጎችን ለማበረታታት መሰረታዊ እና ፖለቲካዊ የሰው ልጆችን ነፃነት የሚያከብር ዲሞክራሲያዊ ስርአት ያስፈልጋል፡፡

ፍፁም አምባ ገነናዊ ወይንም ለዘብተኛ አገዛዞች ዜጎች ለራሳቸው ከሚያውቁት ይልቅ መንግስት አስበልጦ እንደሚያቅላቸው ያምናሉ፡፡ ስለዚህም የዜጎቻቸውን ነፃነት ‹ለዜጎች ጥቅም› ሲሉ ይገድባሉ፡፡ በመጀመሪያ ዲሞክሪያሲያዊ ያልሆኑ ስርአቶች በተፈጥሯቸው ለዜጎቻቸው ‹የሚሻለውን› የመምረጥ ውክልና የላቸውም/ይጎላቸዋል፡፡ ‹ለራሳቸው የማያውቁት› ዜጎች ለነፃነታቸው መነፈግ በእርግጠኝነት አጸፋዊ መልስ ይሰጣሉ – የአጸፋው ዓይነት ይለያይ እንጂ፡፡ እነዚህ አጸፋዎች ከመንግስት ጋር በምንም ጉዳይ ከአለመተባበር/ከመለገም እስከ ትጥቅ ትግል ሊደርሱ ይችላሉ፡፡ ዜጎች የሚሰጡት የአጸፋ መልስ በሀገሪቷ ባሕል፣ ታሪክ፣ ወዘተ… ይወሰናል፡፡ የትኛውም አጸፋዊ እርምጃ ታዲያ የኢኮኖሚ እድገትን በተቃራኒው አቅጣጫ ነው የሚጎትተው፡፡

ጥናቶችስ ምን ይላሉ?

የኢኮኖሚ እድገትን ለማረጋገጥ ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን አምባ ገነናዊ አገዛዝ ያስፈልጋል እና የኢኮኖሚ እድገትን ለማረጋገጥ የሰው ልጆች ተፈጥሮ አንድ አካል የሆነው ነፃነታቸው ወሳኝ ሚና አለው በሚለው ክርክር የመጨረሻ አቋም መያዝ ለተቸገረ ሰው ፊቱን ወደ ጥናቶች ማዞር አማራጭ ነው፡፡

አገዛዞችን በአንድ ወገን፣ ዲሞክሪያሲያዊ ስርአቶችን በአንድ ወገን አስቀምጠው ሀገራትን ከድህነት ለማውጣት የትኛው ስርአት የተሻለ መዝገብ እንዳለው ለመለየት የትየ ለሌ የሆኑ በቁጥር የታጀቡ ጥናቶች ተደርገዋል፡፡ ጥናቶቹ አበክረው የሚያነሱት ጉዳይ ሁሉም አምባ ገነኖች አንድ ወጥ የሆነ ጭቆና (የነፃነት ገደብ) እንደማይፈጽሙ በዛም ልክ ሁሉም ዴሞክራሲያዊ ስርአቶች ሁሉንም ዓይነት (ፖለቲካዊ፣ ግለሰባዊ፣ ወዘተ) ነፃነቶችን በእኩል ደረጃ እንደማይጠብቁ ነው፡፡ ይህንን ከግምት በመክተት ከጥናቶቹ የሚገኘው መረጃ በአጠቃላይ ሲገመገም የሚያሳየው – ሁለቱም ዓይነት የመንግስት ስርአቶች ድህነትን በማጥፋት ረገድ ያላቸው መዝገብ ቅይጥ  መሆኑን ነው – ዴሞክሪያሲያዊም ሆነ አምባ ገነን መንግስት ድህነትን ለማሸነፍ እርግጠኛ እና ብቸኛ መንገድ አይደለም፡፡

የመንግስት ስርአት እንደ ውጨ መጥ (exogenous)?

የአንድ ደሃ ሀገር የመንግስት ስርአት ዴሞክሪያሲያዊ ወይንም አምባ ገነናዊ መሆኑ በራሱ ሀገሪቱን ከድህነት ለማላቀቅ ቀጥተኛ ተፅዕኖ የማይፈጥር ከሆነ የሚሰጠው እንድምታ ምንድን ነው? እውን የስርአቱ ዓይነት ለኢኮኖሚ እድገት ቀመር ውጨ መጥ ነው? ለነዚህ ጥያቄዎች መልስ መስጠት ይከብዳል፡፡ በትንሹ ማለት የምንችለው ግን የዕድገት ምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች የዕድገት ቀመር ውስጥ የሚከቷቸውን ተለዋዋጮች (variables) በተወሰነ ደረጃም ቢሆን የመንግስት ስርአት ተፅዕኖ ያደርግባቸዋል – መጠራጠሩ የሚመጣው የተፅዕኖው አቅጣጫ ላይ ነው፡፡

አዲስ ነገሩ አብይ ተክለማሪያም ይህንኑ ጉዳይ አንስቶ ሲፅፍ የጠየቀውን ጥያቄ ደግሜ ፅሁፌን ልቋጭ፤

“…The question then is this: Do we still find pro-Df [Dabo First] arguments compelling even if we know that we are unable to predict the outcome of giving away our basic liberties with a reasonable degree of certainty?”

‹‹ጥያቄው ታዲያ ይህ ነው፤ ነፃነታችንን አሳልፈን መስጠት ስለሚያመጣው ውጤት በበቂ ደረጃ እርግጠኛ ሳንሆን ‹ዳቦ መጀመርያ› የሚለው መከራከሪያ ውሃ የሚቋጥር ሆኖ እናገኘዋለን?››(ትርጉም የራሴ)

ቸር እንገናኝ!

ጸሀፊውን ለ bemisaleyimiru@gmail.com መልእክት በመላክ ማግኘት ይችላሉ፡፡

About Zone Nine

Zone Nine is a team of writers on Ethiopian social, economical and political situations.

Posted on June 5, 2012, in Sociopolitics. Bookmark the permalink. 6 Comments.

  1. doesn't matter

    Very cute format; what I am not satisfied with is; the “researches” and the analysis’s looks like dawning us to a cyclic questions. I think the columnist “recommendation” is very vital for such papers. Otherwise; a confused person like me, may conclude that(; revolutionary democracy is the ultimate approach on earth.

  2. Thank you for your comment. I endorse your criticism that I should have made my recommendation clearly. But the fact of the matter is that I am undecided on the matter my self. I need to do a pile of reading and get back with an article that tells us – How and Why Non- Democratic regimes alleviated poverty, How and Why Democracies failed to do the same and which success story can be repeated in our country.
    The purpose of this article was not to suggest how democracy is the best in achieving the job, as you pointed out. So, if the Dabo First argument appeals to you more than Freedom first and compel you to think that Revolutionary Democracy is the way forward, then you have a homework to prove your self wrong, when you are done you will enlighten us to get over our dilemma. Which is by the way the very purpose of Zone 9.

    Thank you again! With much respect.

  3. very nicely written piece on the very issue of the days. the issue is coming very controversial not because democracy is not instrumental for development but undemocratic countries like china and Asian tigers are emerging in the world economy competitively. if you have included three and four empirically demonstrable references, the study would have been far convincing.

  4. ታራሚ ነኝ! አመሰግናለሁ!

  5. እኛጋዜጠኞች ያልደፈርነውን እንኳ ደፍረህ እንዲህ መጦመርህ በራሱ በቂ ነው! ያው መቼስ እኛ ሀገር ጀማሪ ትችቱን ካልቻለው ይወድቃል።ምክንያቱም ከስራው ትችቱ ቀድሞ ስለሚጥለን ነው። እንደኔ እይታ ግን የኛ ሰው ትችት ሳይጥልህ ብትጦምር እመርጣለሁ ። አትስማሙም?

  6. አመሰግናለሁ!! ትችቶቹን ገንቢ አድርጎ መውሰድ አስፈላጊ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ተሻሽሎ ለማሳመን ማበረታቻ ናቸው፡፡ ከአክብሮት ጋር!

Leave a comment